Monday, August 12, 2013

የግንቦት ሰባት ንቅናቄ፣ ባለቤት የሌላቸው ታማኝ ሎሌዎች ጉሮኖ ሊሆን አይገባውም! – ከኢትዮጵያ ህዝብ አርበኖች ግንባር የተሰጠ መግለጫ


Image
ላለፉት ስድስት ሳምንታት ያህል በመላው አለም በተለያዩ የዜና መገልገያዎች የዛሬው የግንቦት ሰባት ንቅናቄ መሪ የዶ/ር ብርሃኑ ነጋን ያልተጋነነና ያልተቀጠለ ድምጽ የያዘ ጸረ የኢትዮጵያ ህዝብ አርበኞች ግንባር ንግግር ያላዳመጠው ወገን አለ ማለት የሚቻል አይሆንም። ግመል ሰርቆ ተደብቆ ሆነና ከግራ ቀኙ ጥግ ውስጥ የተከተቱት የድርጅቱ መሪና ባለሞያዎቻቸው ሊሸፍኑት ባይችሉም የበኩላቸውን ምክንያት ይሰጡ ዘንድ በሚል በትዕግስት የጠበቅናቸው ቢሆንም በፊት ለፊትም ሆነ በስተጀርባ ይህን የአፍ መባረቅና የላንቃ መላቀቅ ጉዳይ በተመለከተ አየሁም ሰማሁም የሚል ታማኝ ባለመገኘቱ እንደ ድርጅት ይህን መግለጫ ለማውጣት የተገፋን ሆነናል።ተሸፋፍናችሁ ብትተኙ ገልጬ የማየት ችሎታ አለኝ የሚለውና በአባሎቻችንና በደጋፊዎቻችን ትብብር ጭምር ካዝናው የዳበረው የኢትዮጵያ ሳተላይት ቴሌቪዥን ራስን ነጻ ከማድረግ ይልቅ የቃሉን ትክክለኛነት ባረጋገጠ መልኩ የሰሞኑን የዶ/ር ብርሃኑ ነጋን ጸረ አርበኞች ግንባር ፍካሬ በምን መልኩ በቆሪጥ አይቶ ሊያልፈው እንደፈለገም ለሃገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን እንድናሳውቅ ተገደናል።
የግንቦት ሰባት ንቅናቄ መሪ ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ ንግግር በአጭሩ የኢትዮጵያ ህዝብ አርበኖች ግንባር የሚረባ ድርጅት እንዳይደለ፣ በራሱ ጊዜ የሚፈርስ እንደሆነ ነገር ግን በኤርትራ መንግስት እንደተገለጸው ደሚህት የተባለው ድርጅት ጠንካራ ወታደራዊ ሃይል ያለው፣ ግንቦት ሰባት ደግሞ በሳል ፖለቲከኞች የተሰባሰቡበት በመሆኑ በአስቸኳይ የጋራ ስምምነት ላይ መደረስ እንዳለባቸው እንደተገለጸላቸው ያብራራል። አያይዞም ሌሎቹ የብሄረሰብ ድርጅቶች ለምሳሌም ያህል የቤኒሻንጉልና የጋምቤላ ንቅናቄ ድርጅቶች በሳቸው አመራር ስር በማናቸውም ሰዓት ሊወድቁ እንደሚችሉ ግልጽ በሆነ ቃል ይናገራል። የግንቦት ሰባት መሪ ቃል አክሎም የኢትዮጵያ ህዝብ አርበኖች ግንባር ወደፊት በማናቸውም የዜና አገልግሎት በተለይም በኢሳት ማናቸውንም አይነት የዜና ሽፋን እንዳያገኝ እንደሚያደርጉ የራሳቸውንና የድርጅታቸውን ጠንካራ አቋም ይፋ ያደርጋል።
ዝንጀሮ ወደላይ ከፍ ባለ ቁጥር መቀመጫው ይጎላል እንዲሉ እኛ ከምንናገረው ሂደት ይግለጸው በማለት በኢትዮጵያዊ ጨዋነትና አይን አፋርነት የግንቦት ሰባት መሪዎችንና “ከሰማየ ሰማያት ወርጄ፣ ከወያኔ ጉያ ወጥቼ አድንሃለሁ!”ለሚለው የመሲህ ቋንቋቸው ጆሮ ሰጥተን ባናውቅም ዶ/ር ብርሃኑና ግብረአበሮቻቸው የጀመሩት መንገድ እሾሃማ ነውና አይ በቃችሁ ልንላችሁ ተገደናል።
ወጣቱን ትውልድ “ውጣ ግደል ተጋደል! ለእናት ሃገርህ ሙት” በማለት በማያውቀው መንገድ ለእሳት ሲዳርጉት የነበሩት የደርግ ሹማምንት ጦርነቱ ግሞ ሙቀቱ ከፍ ሲልና መውጫ መግቢያ ሲጠፋቸው “ጦርነቱ ቆሟል መሳሪያህን አስቀምጥ!” በማለት ጸረ ሃገር ለሆነው ወያኔ እጁን አስይዘው እነሱም ተዋርደው ዘብጥያቸው መውረዳቸውን አስተውለናል። የትላንቶቹ የግንቦት 20 አምላኪዎችና የ2005ቱ የግንቦት 7 እጩ ተወዳዳሪዎች እነ ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ የቋመጡትን ስልጣን ሲያምራችሁ ይቅር ሲባሉና የሚገባችሁ ስፍራ ዘብጥያ ነው ተብለው እቅጩ ሲነገራቸው ሊሞትላቸው የወጣን ወጣት ደም ክደው “ጥፋተኞች ነን” በማለት በነጻነት መሪዎች ታሪክ ባልታየ መልኩ ህዝብንና ታሪክን ሸውደው “ጥፋተኛ ነን” በማለት በፊርማቸው አረጋግጠጠው ነጻነታቸውን ሲያገኙ “እግዚኦ ያንተ ያለህ” በማለት ተገረምን እንጂ የታባታችሁ አላልንም።
መተኪያ የሌላቸው የኢትዮጵያ ምሁራን በዘረኛው ወያኔና በነዶ/ር ብርሃኑ ነጋ ትብብር ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተመንጥረው ሲባረሩ እያወቅን ቂም ቋጥረን አልመከርንም አልዘከርንም።
በመሰረቱ ዶ/ር ብርሃኑ ነጋና ጥቂት ተባራሪዎቻቸውን ከፍጥረታቸው አንስተን ዛሬ ራሳቸውን አንቱ ብለው እስከጠሩበት ጊዜ ያለውን ሂደት በውሉ ለምናውቀው የኢትዮጵያ ህዝብ አርበኞች ግንባር ተዋጊዎች፣ የዛሬው የሳቸው “ዘራፍ የግንቦት አሽከር!” ፍካሬ ባያስደንቀንም ቢያንስ ላለፉት አስር ዓመታት ደማቸውን እያፈሰሱ ያሉ አርበኞችን ያፈራ ድርጅት አካል መሆናችንን በመገንዘብ ሰብዕናን የተላበሰ ፣ የመሪነት ብቃት ያለው ቋንቋና ቃላት መምረጥ የሚችል አዕምሮ ይኖራቸዋል ብለን ማሰባችን አልቀረም። አለመታደል ሆኖ ግን አብሮ ስለመስራትና ስለቅራኔ አፈታት ማን ቢወልድ ማ አይሳናቸውም ተብሎ በደጋፊዎቻቸው የሚነገርላቸው ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ ቅማል ሽቅብ ይጋለብ ይመስል አንድ “ተጋዳላይ” ከእንግሊዝ ሃገር መልምለው ወደ በረሃ በላኩ በወሩ በድርጅታችን ላይ ጦር መስበቃቸው እጅጉን አስገርሞናል።
ትላንት “ጦርነት የፋራ ነው! “ “ከሻቢያ ጋር መስራት ጸረ ሃገር ነው!” እያሉ በወያኔ ቤተ-መንግስት ውስጥ ከነበረከት ስምዖንና ታምራት ላይኔ ጋር ሲሳለቁብን የነበሩት የዛሬው ተጋዳላይ ዶ/ብርሃኑ ነጋና ግብረ አበሮቻቸው፣ በወያኔው የቤተ-መንግስት የጨረቃ ግባት ጠብ የሚል ነገር እንደሌለ በተነገራቸው በአስረኛው አመት እየተሽኮረመሙና በጥቁር ነጠላ ተሸፋፍነው ካለንበት በረሃ ሶስት ሁነው ስናገናቸው አልተቀየምንም።
በግንቦት ወር ዝንብና ንብ እንደሚመሳሰል እያወቅን ነገር ግን የጋራ ትግል አስፈላጊነቱን ከግምት ውስጥ በማስገባት በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ትብብርና ጥያቄያችንን ብናቀርብም አብረን እንስራ ቀርቶ ” በሻቢያ ከሚደገፉና ከሽብር ፈጣሪነት ከተመደቡ ቡድኖች ጋር አብረን መስራት አንችልም” በማለት በተወካያቸው አማካይነት መልክት የሰጡን የግንቦት ሰባቱ መሪ ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ ምላሽ ቅር ቢያሰኘንም አኩራፊና አጥፊ ሆነን አልፈከርንም። ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ ከውልደቱ አንስቶ እስከዛሬ ድረስ ለኢትዮጵያዊነትና ለኢትዮጵያውያን ውርደት ታክቶ ይሰራ ከነበረው የወያኔው ቀንዲል መለስ ዜናዊ ጋር በአዲስ አበባ ቤተ-መንግስት ያለገደብ እየሳቁና እየተሳለቁ የፎቶግራፉን አምድ ሲያጣብቡት የነበሩትን ያህል ስለ ዴሞክራሲና እየተገደለ ስላለው ህዝብ አስበው ለአንዲት ቀን እንኳን ከበረሃችን ተገኝተው የምንበላውንና የምንጠጣውን ብሎም የምንተኛበትን ታዛ ሊያዩልን ስላልወደዱ አላኮረፍንም።
ዛሬም ድረስ እንደ አባይ ጠንቋይ ተሸፋፍነው “እንታገላለን! የወታደር ሃይል አለን! ከወር በኋላ አዲስ አበባ እንገባለን!” የሚሉት ዶ/ር ብርሃኑ ነጋና ተባባሪዎቻቸው ከደጋፊዎቻቸው የሰበሰቡትን ሂሳብ በቀላሉ ማወራረድ ይችሉ ዘንድ ” ዘራፍ የግንቦት አሽከር!” ሲሉ እየሰማን የኮረኮሩንን ያህል መሳቅን እንጂ መተናኮልን ለአንዲት ቀን አስበነው አናውቅም።
“የሻቢያ አሽከሮች እያሉ!” በሰብዕናችንና ኢትዮጵያዊ ጨዋነታችን ላይ የተሰማሩብን ዶ/ር ብርሃኑ ነጋና ፈተው የሚለቁብን በጣት የሚቆጠሩ ታማኞቻቸው የረገጥነውን በረሃ ረግጠው የኢትዮጵያን ህዝብ ለነጻነቱ ለማብቃት ብቃቱና ወኔው አላቸው ብለን አልመነው ባናውቅም የጠላቴ ጠላት ወዳጄ ነው በሚለው የቂል ፖለቲካ ስንመራ የኖርን መሆናችንን ለአንዴም መደበቅ አንወድም።
በመጽሃፋቸው ሽፋን ላይ ሳይቀር በሃገራችን ኢትዮጵያ ዴሞክራሲ እንደነበረና ሊቀለበስም እንደተሞከረ የሚደሰኩሩን አፍቃሬ ህወሃቱ ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ፣ ቢያንስ ካለፉት 10 አመታት የትግል ተሞክሯችን በመነሳት ከህዝባዊ ወያኔ ሃርነት ትግራይ ጋር በሚደረግ የትግል መሬት ላይ ፎጣ እንጂ ቦምብ ሊወረውሩ ብቃት እንደሌላቸው ከመመስከር ወደኋላ አንልም።
ጸሎትና አርበኝነት ለታይታ አይደለምና የሙታን ሰማዕታቶቻችንን ምስልና ታሪክ ማቅረብ ብንችልም ከጦርነቱ ወላፈን የተነሳ ፕሮፌሰሮች፣ ጀኔራሎችና የወታደራዊ ሳይንስ ሊቃውንቶች ሊኖሩም ባይፈቅድም፣ በአላማቸው የጸኑ፣ለድርጅት ዲሲፕሊን ተገዢ የሆኑ፣ከንጋት ጀምሮ ወያኔን ሳያወላውሉ በሚታገሉ አርበኞች አመራር ተደራጅተን የምንታገል የህዝብ ልጆች መሆናችንን ምንጊዜም ከማስገንዘብ ወደኋላ አንልም።
በመሆኑም እኛ የኢትዮጵያ ህዝብ አርበኞች ግንባር አባላት ሰሞኑን ከዶ/ር ብርሃኑ ነጋ በተሰራጨው ንግግር የተነሳ የተሰማን ቅሬታና ቁጣ ጊዜ በቀላሉ የሚፍቀው አለመሆኑን ለመግለጽ ከመውደዳችን በተጨማሪ ለአባላቱና ለደጋፊዎቹ እንዲሁም “ነጻ የዜና አገልግሎት ነው” በሚል አባሎቻችን ጭምር ላይታች ይሉለት የነበረው ኢሳት
- ራሳቸውን ከዶ/ር ብርሃኑ ነጋና ግብረአበረቻቸው በማራቅ የህዝብ አገልጋይነታቸውን እንዲያሳዩ፡
- የተሰባሰቡበት ግንቦት ሰባት የተባለው አካል በጠንካራ መሪዎች ተዋቅሮ ከዴሞክራሲያዊ ሃይሎች ጋር ከልብ ለመስራት እንዲመክሩ
- የህዝብ ደም አላግባብ መፍሰስ አስቆጥቷቸው ግንቦት ሰባት ከተባለው ቡድን ውስጥ መጠለያ የወሰዱ ታጋዮች መኖራቸውን የምናውቅ በመሆኑ እኒህ የህዝብ ልጆች በላያቸው የተቀመጡባቸው መሪዎቻቸው እንደጋሪ ፈረስ ጥርሳቸውን እያጣመሙ ወደፈለጒበት አቅጣጫ ሲዘውሯቸው መመልከት አያሳቸውና ከተኙበት እንዲነቁ
- ምራቃቸውን ዋጥ ያደረጉ፣የአነጋገር ለዛ ያላቸውና ቢያንስ በመራሄ ድርጅትነት የተሟላ ተሰጥዖ አላቸው የሚባሉ መሪዎችን በአመራር ላይ በማስቀመጥ ጀግንነት፡ አርበኝነትና ተጋዳይነት ካለበት ስፍራ ይገኙ ዘንድ ግፊት እንዲያደርጉ ጥሪ ሲያደርግ
- ኢሳት የተባለው የዜና አገልግሎትም እውን ከግንቦት ሰባት ባለቤትነት ነጻ የሆነና ሁሉንም ታጋይ ሃይሎች በእኩል የሚያገለግል አውታር መሆኑን ይፋ እንዲያደርግና ሰሞኑን የግንቦት ሰባቱ መሪ ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ እንደግል ሱቃቸው ሊያዙት እንደሚችሉ ባሰሙት ንግግር ዙሪያ የኢሳት የቦርድ አባላትም ሆኑ ተራ ጋዜጠኞቹ
ይፋ ወጥተው መግለጫ ይሰጡ ዘንድ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን።

አንድነት ሃይል ነው!
የኢትዮጵያ ህዝብ አርበኞች ግንባር
ነሃሴ 5 ቀን 2005 ዓ/ም

1 comment:

  1. I can't say it more than that,you know I am always wonder why after all these years we can't learn from our mistakes? what kind of Azim we are in? it so sad, why we never learn from our mistake.our peoples are dying, the country's situation is getting worst every day. what happen to us guys can you stop for a moment and thing what you are doing? weather you believe or not there is nothing come out from Addis abeba and Washington DC politician to me they are equally criminal like Woyane no less.
    .

    ReplyDelete