Thursday, August 8, 2013

ታማኝ በየነ እና ቴዲ አፍሮ ከአመታት በኋላ መድረክ ላይ ተገናኙ

“ጥቁር ሰው” በድጋሚ ሲዘፈን ሌላ የሚያስጮህ ነገር እንደሚመጣ ያልጠበቀው የአውሮፓ ታዳሚ፤ ጉሮሮው እስኪነቃ እንደገና ጮኸ። ታዳሚው ከፊት ወንበር ላይ በVIP ላይ ታማኝ በየነ መቀመጡንም ሆነ፤ በስፍራው መገኘቱን አያውቅም። ቴዲ አፍሮም “ጥቁር ሰው”ን እንደገና ከማቀንቀን ውጪ፤ የድሮ ጓደኛው ወደ መድረክ ይመጣል ብሎ አልጠበቀም። የሆነው ግን እንዲህ ሆነ።
ሁለቱም ኢትዮጵያ ያፈራቻቸው የዘመኑ እውቅ አርቲስቶች ናቸው – ታማኝ በየነ እና ቴዲ አፍሮ።
ከአመታት
በፊት የነበረው ወዳጅነታቸውን ግን እንደድሮው ለማየት ያልታልን አድናቂዎቻቸው፤ በልባችን “ግን ለምን?” እያልን
መቆጨታችን አልቀረም። በተለይም ቴዲ አፍሮ ታስሮ በነበረበት ወቅት፤ ታማኝ በየነ “Free Teddy Afro” በሚል
ይሰራ የነበረውን አካል በማንቀሳቀስ ጉልህ ሚና መጫወቱ ይታወሳል። በዋሺንግተን ይደረጉ በነበሩ ሰላማዊ ሰልፎች
ላይ በመገኘት ጭምር ስለቴዲ ነጻ መሆን ቅስቀሳ አድርጓል።
ኢ.ኤም.ኤፍ. ባለው ሌላ የቪዲዮ መረጃ ታማኝ በየነ፤ “ጃ ያስተሰርያል” የሚለውን የቴዲን ዘፈን ግጥም በመቀየር፤ “ጃ
ቴዲ ይፈታ!” በማለት ሌሎቹንም ግጥሞች ጭምር፤ ቴዲ አፍሮ ነጻ መሆን እንደሚኖርበት በሚገልጽ መልኩ ሲዘፍን
ህዝቡም የለቅሶ ያህል፤ ታማኝን አጅበው ሲዘፍን የነበረው ሁኔታ የቅርብ ጊዜ ትዝታችን ነው። ሆኖም ከአመት በኋላ
ቴዲ አፍሮ ከተፈታ በኋላ ግን፤ በግልም በመድረክም ላይ ከነታማኝ በየነ ጋር ልናያቸው አልቻልንም። በመሃላቸው
ምንም አይነት መቀያየም ወይም መጠላላት ሳይኖር፤ እኛም እንደድሮው አንድ ላይ ሳናያቸው፤ አይናችንን ፍቅር
እንደራበው 2013 ገባ።
በዚህ አይነት ዝምታ ወራት አልፈው አመታት ተቆጠሩ። በአውሮፓ በሚደረገው አመታዊ የኳስ ጨዋታ ላይ፤
በመዝጊያው ምሽት ቴዲ አፍሮ ሊጫወት መጥቷል። ታማኝ በየነም ወደ አውሮፓ ሄዶ ነበርና የቴዲ አፍሮን የመዝጊያ
ዝግጅት ላይ፤ በክብር እንግድነት እንዲገኝ በነክንፉ በኩል ግብዣ ተደርጎለት በስፍራው ተገኝቷል። ዘፈን አልፎ ሌላ
ዘፈን ተተካ… “ጥቁር ሰው”ም ተዘፈነ።
“ጥቁር ሰው” ሲዘፈን ህዝቡ አብሮ ይዘፍናል… “ምኒልክ ጥቁር ሰው” እያለ ቴዲ አፍሮን ያጅበዋል። ዘፈኑ ካለቀ
በኋላ እንደገና እንዲዘፈን ህዝቡ ጥያቄ አቀረበ። ቴዲ አፍሮ ጥቁር ሰውን እንደገና መጫወት ጀመረ። ህዝቡ ደስታውን
ገለጸ። በድጋሚው ሲዘፈን ሌላ የሚያስጮህ ነገር እንደሚመጣ ያልጠበቀው የአውሮፓ ታዳሚ፤ ጉሮሮው
እስኪነቃ እንደገና ጮኸ።
ታዳሚው ከፊት ወንበር ላይ በVIP ላይ ታማኝ በየነ መቀመጡንም ሆነ፤ በስፍራው መገኘቱን አያውቅም። ቴዲ አፍሮም
“ጥቁር ሰው”ን እንደገና ከማቀንቀን ውጪ፤ የድሮ ጓደኛው ወደ መድረክ ይመጣል ብሎ አልጠበቀም። የሆነው ግን
እንዲህ ሆነ።
ቴዲ አፍሮ “ምኒልክ ጥቁር ሰው”ን እያቀነቀነ ሳለ፤ ታማኝ በየነ የኢትዮጵያን ሰንደቅ አላማ ይዞ ወደ መድረኩ ወጣ።
ህዝቡ ታማኝ በየነን ባልጠበቀው ጊዜና ቦታ ላይ ማየቱ ብቻ ሳይሆን፤ ጠቅላላ ሁኔታው በቁሙ አደነዘዘው… ብዙዎች
በደስታ ሲቃ ጮኹ፤ አንዳንዶች በደስታ አለቀሱ። ታማኝ በየነ እና ቴዲ አፍሮም እንደገና የኢትዮጵያን ሰንደቅ አላማ፤
አንድ ላይ በአንድ መድረክ ላይ አውለበለቡ! የጽሁፍ ዘገባችን አበቃ። በቪዲዮ ለተቀረጸው ዝግጅት የስራ
ባልደረባዬ ክንፉ አሰፋን በመጋበዝ የኔ ዘገባ እዚህ ላይ ያበቃል።
(ዳዊት ከበደ ወየሳ – አትላንታ)

No comments:

Post a Comment