Sunday, August 4, 2013

ኢህአዴግ ተገፍቶ እንጂ አስቦ አይሰራም ! በቀላጤ የሚመራን መንግስት ማመን…

ሀ.ኢህአዴግ ተገፍቶ እንጂ አስቦ አይሰራም የሚል አቋም ከያዝኩ ከራርሚያለሁ፡፡ በመሆኑም ኢህአዴግን መግፋት(Pressurize ማድረግ) ዲሞክራሲ ማስፈን ባይቻልም ልማት ላይ ግን የተወሰነ ለውጥ ማስመዝገብ ይቻል ሆናል ብየ ሳስብ ነበር፡፡ ለዚህ አስተሳሰቤ ደግሞ አዲስ አበባን እንደ ማስረጃ አቀርብ ነበር፡፡ አዲስ አበባ በ1993 ባሳየችው ድንገተኛ አመፅ ጀርባው አዙሮባት የነበረውን ኢህአዴግን አባንና ትኩረት አገኘችና በአቶ አባይ ፀሃየ የሚመራ የጥናት ቡድን አቋቁሞ ለተግባራዊነቱ ደግሞ አቶ አርከበን ከትግራይ ሊያስጠራ ችሏል፡፡ በዚህ መሰረት የከተማ ድህነት ባይቀርፍም በመንገድና በህንፃ ግንባታ እና በተወሰነ መልኩም በመንግስታዊ መስሪያ ቤቶች ለባለ ጉዳዮች የሚሰጥ መስተንግዶ ላይ መሻሻል ታይቷል፡፡
ሰሞኑን ግን ይኸንን አስተሳሰቤን ለመከለስ ከራሴ ጋር ሙግት ገጥሚያለሁ፡፡ ለክለሳየ ምክንያት የሆኑኝ የሚከተሉት ናቸው፡-
1. የባቡር መስመር ዝርጋታ የኢህአዴግን ተገፍቶ መስራት ጉዳቱን አጋልጦታል፡፡ የባቡር መስመር ያልፍባቸዋል ተብሎ በታቀዱት አካባቢዎች የሚታየው የሃገር ሃብት ውድመት የባቡር ሃዲዱ ግንባታ የታቀደው መቼ ነው? የሚል ጥያቄ ያስነሳል፡፡ ሌላው ይቅርና ብዙ ሚልዮን ብር ፈሶባቸው በቅርብ የተሰሩት መንገዶች እንደገና ሲፈርሱ ማየት ከተማዋ ማስተር ፕላን የላትም? በፕሮጀክቶችና በአስፈፃሚ መስሪያ ቤቶች መካከል መናነብ የለም? ያስብላል፡፡ ጎተራ ያለው አደባባይ ሲሰራ የባቡር ሃዲድ መስመር የሚያሳይ ነገር ነበረው፡፡ ነገር ግን በዛ መስመር ከአደባባዩ በኋላ የተሰራ መንገድ የባቡር ሃዲድ ለመስራት እንደጋና እየፈረሰ ነው፡፡ ለዚህ የሃገር ሃብት ውድመት፤ የኛ የነዋሪዎች በመንገዶች መፍረስና መልሶ መገንባት ምክንት ለሚደርስብን እንግልት ሃላፊነት የሚወስደው ማነው? በመሿለኪያ ሳልፍ በቅርብ የተገነባውን ድልድይ እያየሁ ምን እድል ያጋጥመው ይሆን? እሱም ሊፈርስ ? ለመገንባት ስንት ሚሊዮን ብር ወጥቶበት ይሆን? ወዘተ እያልኩ እጠይቃለሁ፤ እሳቀቃለሁ፡፡ እስቲ ከሳሪስ በኩል የሚመጣው ባቡር እንዴት ሊያልፍ እንታቀደ የምታውቁ ካላችሁ መረጃ አካፍሉን፡፡ ወደ መገናኛ ስሄድ የቀለበት መንገዱ ድልድይ ከስሩ እየተቆፈረ ነው፡፡ ቀለበት መንገዱ ሲሰራ ባቡር አልታሰበም ነበር? ወዘተ፤ወዘተ፤ጨምሩበት፡፡
2. ህንፃዎች እጅብ ባሉበት አካባቢ ስሄድ ጭንቀት ይፈጥርብኛል፡፡ በጣም ጥቅጥቅ፤ትፍግፍግ ያሉ ስለሆነ በዚያ በኩል ማለፍ ጭንቀት ይፈጥራል፡፡ በዚያ ላይ መኪናና እግረኛ እየተጋፉ ነው የሚሄዱት፤ የሰውና የተሽከርካሪ መንገድና መቆሚያ አልተለየም፡፡ በመሆኑም አዲስ አበባ ለነዋሪዎቿ የማትመች ከተማ እየሆነች ነው ማለት ነው፡፡ ተገፍቶ የመስራት ውጤት
3. ድሮድሮ በየሰፈሩ፤በየከፍተኛው የስፖርት (በተለይ የእግር ኳስ) ማዘውተሪያ ስፍራዎች ነበሩ፡፡ አሁን ቦታዎች ኮንደሚንየም ተሰርቶባቸዋል፤ አልያ ደግሞ ኪስ ቦታ እየተባሉ ለቱባ ባለስልጣኖች ተሰጥተው ቤት ተገንብቶባቸዋል፡፡ በዚህ መሰረት መተንፈሻ ቦታ እየጠፋ ነዋሪዎቿ ምቾት አልሰማ ብሎናል፡፡ ከተማ ደግሞ ለነዋሪዎቿ ምቹ ካልሆነች ግንብ ቢደረደር ጥቅሙ ምንድን ነው፡፡
4. የዚህ ሁሉ ተጠያቄ መሃንዲሶቻችን ወይስ ፖለቲከኞች የሚል ሳሰላስል ቆየሁና ሰሞኑን ግን አንድ የሚያስደነግጥ ፍንጭ አግኝቼ በቀላጤው የኢህአዴግ መንግስት የነበረኝን አሉታዊ አስተሳሰብ አጠነከረልኝ፡፡ ጉዳዩ እንዲህ ነው፡፡ የጀሞ ኮንዶሚንያም ዘሞ ነዋሪዎቹ እንዲወጡ ተደረጉ የሚል ወሬ ስንሰልቅ በመሃከል መሃንዲሶች አፈሩ ዋርካ ስለሆነ ጥልቀት የሌለው ግንባታ ቢከናወን አደጋ ያመጣል የሚል ሪፖርት አቅርበው በፖለቲካ ዉሳኔ ነው የተገነባው የሚል ስሰማ እጤ ዱብ አለ፤የቀላጤው መንግስት ፖለቲከኞችም ረገምኩ(ለመረጃው ቅርበት ያላችሁ ሰዎች የዚህ ነገር እርግጠኛነት እስቲ አካፍሉን)፡፡
5. እናንተም አክሉበት
ለ. መንግስት የመኖሪያ ቤት ችግር ለመፍታት(ዳያስፖራዎች በእቅዱ ሲካተቱ የምን ችግር ለመፍታት እንደታሰበ ባይገባንም፤ ደግሞ እኮ ከየትም ክልል የሄደ ዳያስፖራ በፕሮግራሙ የመታቀፍ መብት አለው፡፡አገር ወስጥ ካለው የክልል ነዋሪዎች የተለየ መብት ለምን እንደተሰጣቸው በገንዘብና በድጋፍ ድርቅ የተመታው ኢህአዴግ ብቻ መሰለኝ የሚያውቀው) የነዋሪዎችን የገቢ ሁኔታ ግምት ውስጥ ያስገባ ፕሮጀክት ቀርጫለሁ ብሎ ባወጀው መሰረት እኔም በወገንና በእጅ ለማይሄድ ሰው የትኛው ያዋጣል ብየ አሰብኩና በማህበር መደራጀት የተሻለ አማራጭ ሆኖ አገኘሁት፤ በዛ መሰረት ለመደራጀት ወደ ክፍለ ከተማ ጎራ አልኩ፡፡ በክፍለ ከተማው ሰራተኞችም(ቀድሜ በቴሌቪዥን የሰማሁትም ቢሆንም) ያሉት የአደረጃጀት ኤነቶችና የቤት አማራጮች በተመለከተ ማብራሪያ ሰጡኝ፡፡
የአደረጃጀቱ አይነት ሀ. በማስፋፊያ ለ. በመልሶ ማቋቋሚያ
- በማስፋፊያ ህንፃዎቹ G+2 ሆነው ሁለት አይነት አማራጭ ፕላኖች ቀርበዋል፡፡የቤቱ አይነት ባለ አንድ፤ሁለትና ሶስት መኝታ፡፡ መኖሪያ ህንፃዎቹ የሚሰሩት በከተማዋ ዳር ነው ተባልኩ፡፡
-በመልሶ ማቋቋሚያ የሚሰሩ ህንፃዎች G+4 ሆነው ሶስት አይነት አማራጭ ፕላኖች ወይም የህንፃ ዲዛይኖች (እነሱ Typologies ይሏቸዋል) ቀርበዋል፡፡ የቤቱ አይነትም ባለ አንድ፤ሁለትና ሶስት መኝታ ነው፡፡ ሁሉም ህንፃዎች ከሚከፈለው ጠቅላላ ዋጋ ውስጥ የሚካተት የማህበርተኞች የምድር ቤት ሱቆች አሏቸው፡፡ የመልሶ ማቋቋሚያ ለተፈናቃዮች ካሳ የሚከፈል ተጨማሪ ወጪ ይኖረዋል፡፡ ስንት እንደሆነ ግን አይታወቅም፡፡ ቀላጤው መንግስት ምን ያህል እንደሚተምንበት ደግሞ ከወዲሁ መገመት ያዳግታል፡፡
እንግዲህ ልብ በሉ መንግስት በጉዳዩ ካሰብኩበት ቆይቷል፤ ዝግጅቴን አጠናቅቂያለሁ ብሎ ለፍፏል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ህግ ደንግጓል፤ የአደረጃጀት ደንብ አውጥቷል፤ሰራተኞችን አሰልጥኖ አሰማርቷል፡፡
በወጣው ህግ መሰረት በአባላቱ መሃከል ቀድሞ ትውውቅ ባይኖረንም በክፍለ ከተማው ተገኝተን 24 አባላት ያሉበት ማህበር ለመመስረት ተስማማን፤ በአደራጆቹ ገለፃ ተደረገልንና በሰነዶች ላይ ተፈራረምን፤ የማህበራችን ስም ሰየምን፡፡ የቀረው ነገር ከክፍለ ከተማው ድጋፍ ደብዳቤ ይዞ ወደ ንግድ ባንክ በመሄድ በማህበሩ ስም አካውንት መክፈት ነው፡፡ይኸ ሁሉ የተሰራው አንዳንድ ግር ያላቸው ነገር ካለ የክፍለ ከተማው ሰራተኞች ከሚመለከታቸው አስፈፃሚ አካላት ጋር እተደዋወሉ ነው፡፡የወከልናቸው ሰዎች እኛን በሶስት ሰአት ባንክ ተገኙ ብለው የድጋፍ ደብዳቤውን ለማውጣት በጠዋቱ የስራ ሂደት ሃላፊው ቢሮ ይሄዳሉ፡፡ ሃላፊው ስብሰባ ተጠርተው ሄደዋልና በ7፡30 ተኩል ተመለሱ ታባሉ፡፡ እንደተባሉት በሰባት ተኩል ሲሄዱ ግን ያልታሰብ ዱብ እዳ ገጠማቸው- አዲስ መመሪያ ወጥቷል የሚል፡፡ ለወራት ታስቦ፤ታቅዶ የተዘጋጀን ነገር በአንድ ስብሰባ ተሽሮ አዲስ አሰራር ወጥቷል ተባለ፡፡በዚህ መሰረት፡-
- 60 ካሬ ሜትር ስፋት የነበረው ባለ አንድ መኝታ ቀርቷል፡፡
- 60 ካሬ ሜትር ስፋት የነበረው ባለ አንድ መኝታ ካሬ ሜትሩ ለውጥ ሳይደረግበት ባለ ሁለት መኝታ እንዲሆን ተወስኗል
- 80 ካሬ ሜትር ስፋት የነበረው ባለ ሁለት መኝታ ካሬ ሜትሩ ለውጥ ሳይደረግበት ባለ ሶስት መኝታ እንዲሆን ተወስኗል፡፡ ክፍያውም ከ280 ሺ ወደ 350ሺ ከፍ እንዲል ተደርጓል፡፡
- 110 ካሬ ሜትር ስፋት የነበረው ባለ ሶስት መኝታ ካሬ ሜትሩ ለውጥ ሳይደረግበት ባለ አራት መኝታ እንዲሆን ተወስኗል(በፊት ባለ አራት መኝታ የሚባል አልነበረም)፡፡ ክፍያውም ከ385 ሺ ወደ 476ሺ ከፍ እንዲል ተደርጓል፡፡
- ምድር ቤት የሚኖሩት ሱቆች ለያንዳንዱ ማህበርተኛ በመረጠው የቤት አይነት እንዲከፋፈሉ ተደርጓል፡፡ ለምሳሌ ባለ አራት መኝታ 26 ካሬ ሜትር፤ባለ ሶስት መኝታ 20 ካሬ ሜትር ሱቅ ይኖረዋል ማለት ነው፡፡ ሁሉም ነዋሪና ሁሉም ህንፃዎች ሱቅ ስለሚኖራቸው የሱቆቹ የገበያ ሁኔታ እግዜር ይወቀው፡፡
ይኸን መርዶ ስሰማ በኢህአዴግ ላይ ይበልጥ እምነት አጣሁ፤ ጊዜ፤ጉልበትና ሃብት ወጥቶበት የተዘጋጀ ህግን እንዴት በአንዲት ስብሰባ በቀላጤ ይለውጠዋል ብየ ጭሰስስስስ አልኩላችሁ፡፡አንድ ነገር አስታወስኩኝ፡፡ የመመረቂያ ፅሁፌን ለማዘጋጅት ወደ መንግስት ቢሮዎች ስመላለስ ስለ ውጤት ተኮር አሰራር ጠየቅኳቸውና እሱኮ ቀርቷል፤አንጠቀምበትም አሉኝ፡፡ በቀድሞ አጠራሩ ሲፒኤ ተብሎ የሚጠራው የስቪል ሰርቪስ መስሪያ ቤት ሄጄ ስጠይቅ ደግሞ አሰራሩ አሁንም አለ፤አልተሻረም የሚል መልስ አገኘሁ፡፡ ታዲያ መስሪያ ቤቶች ለምን አንሰራበትም፤ተሽሯል አሉኝ ስላቸው፤ እሱ ነገር ያጋጠመው አቶ ተፈራ የለውጥ አመራር አባላት ሰብስቦ ውጤት ተኮር ትተነዋል፤ይቁም ስላለ ነው፡፡ እኛ ደግሞ በሚኒስትሮች ምክር ቤት የወጣ ደንብን አንድ ሚኒስቴር ከመሬት ተነስቶ ተሰርዟል ስላለ አንሽረውም፤ ህጉን ያወጣው አካል ስለመሻሩ በፅሁፍ ያሳወቀን ነገር የለም የሚል መልስ ተሰጠኝ፡፡ ያም ሆነ ይህ አቶ ተፈራ በቀላጤ የሻሩ የፀና ሆኖ ውጤት ተኮር መስሪያ ቤቶቹ መጠቀም አቆሙ፡፡    http://freedom4ethiopian.wordpress.com/2013/08/03/4654-2/
እና አሁን የምጠይቃችሁ ከእንዲህ አይነቱ በግብታዊነት፤በቀላጤ፤ በአሰራር ሳይሆን በፖለቲካዊ ውሳኔ የሚመራ መንግስት ጋር አምኖ ውል መግባት ይቻላል ትላላችሁ? አሁን በጨመረው ዋጋ ላይ በመንግስት የሚተመን የተፈናቃይ ካሳ ክፍያ፤ የግንባታ መሳሪያዎች የዋጋ ጭማሪ ማስተካከያ፤ የቤቱ ፍኒሺንግ ደግሞ ተጨማሪ ወጪ ነው፡፡ 40/60 ተመዝጋቢው ብዙ ሊሆን ይችላልና ለምርጫ ሲል ላይነካካት ስለሚችል(እጣ መድረሱ በእጅና በዘመድ/እውቂያ ካልሄዱ ሊያስቸግር እንደሚችል እንዳለ ሆኖ) እሱን እንደ አማራጭ ልውሰድ? ምን ትመክሩኛላችሁ፡፡
ከግብታዊ፤በቀላጤ ከሚመራና ከማይታመን መንግስት ይሰውረን

No comments:

Post a Comment