Thursday, June 6, 2013

ከሰማያዊ ፓርቲ የተሰጠ መግለጫ (መንግስት ለሕዝብ ጥያቄዎች ምላሽ እንዲሰጥ አሁንም እንጠይቃለን!)

ማያዊ ፓርቲ
ሰማያዊ ፓርቲ የጠራው ታላቅ ሰላማዊ የተቃውሞ ሰልፍ ግንቦት 25 ቀን 2005 ዓ.ም በርካታ ሕዝብ በተገኘበት ደማቅ ሆኖ ተካሂዷል፡፡ ለዚህ ሰልፍ መሳካት ከፍተኛ ድጋፍና አስተዋፅኦ ላደረጉ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ የሲቪክ ማህበራት፣ የመገናኛ ብዙኃንና በሰልፉ ለተሳተፉ ዜጎች እንዲሁም ሰልፉ በሰላም እንዲጠናቀቅ ለረዱ የፀጥታ ኃይሎች ፓርቲያችን ልባዊ ምስጋናውን ያቀርባል፡፡Blue Party Ethiopia
ከዚህ በተቃራኒ ግን ይህንን ሰላማዊ የተቃውሞ ሰልፍ ተከትሎ የገዥው ፓርቲ ባለስልጣናትና የመንግስት ተወካዮች የተለመደውን ተልካሻ አስተያየቶች ሰጥተዋል፡፡ የገዥው ፓርቲ ተወካይ ሰልፉን አስመልክቶ በሰጡት አስተያየት “የሐይማኖት አክራሪነት አጀንዳው አድርጎ ሲንቀሳቀስ የነበረው ሰማያዊ ፓርቲ ዛሬ በጠራው ሰላማዊ ሰልፍ ድብቅ አጀንዳው ገሃድ ወጣ” በማለት በሰጡት አስተያየት ፓርቲውን ለማንቋሸሽና ለማራከስ ሞክረዋል፡፡ ይህም ፓርቲውን በእጅጉ ያስቆጣ ነው፡፡ ይህ ዓይነቱ መሰረተ ቢስ ፍረጃ የገዥው ቡድን አባላት ለንግግራቸውና ለሚሰጡት አስተያየት ሚዛን የሌላቸው ከመሆኑ ውጭ በፓርቲው ፕሮግራምም ሆነ እንቅስቃሴ ከአሸባሪነት ጋር የሚያገናኘውን አንዳችም ነገር አልጠቀሱም፡፡ ፓርቲው በሕጋዊ መንገድ ተመዝግቦ እየተንቀሳቀሰ የሚገኝ እና በሕገ መንግስቱ በተሰጠው መብት ተጠቅሞ በሕጋዊ ሥነስርዓት ያደራጀውን ሰላማዊ የተቃውሞ ሰልፍ በእንዲህ አይነት መንገድ መፈረጅ ሰልፉ ከተጠራበት ዓላማና መንፈስ በእጅጉ የራቀ አስተያየት ሆኖ አግኝቶታል፡፡
ፓርቲው ከዚህ በፊትም በተደጋጋሚ በሰጣቸው መግለጫዎች በእስልምና እምነት ተከታዮች ላይ የሚደረገውን ጣልቃ ገብነት መቃወሙ ይታወሳል፡፡ ይህንኑ ጥያቄ በተቃውሞ ሰልፉ ላይ ወደ አደባባይ ይዞ መውጣቱ ሕገ መንግስታዊ የመብት ጥያቄ መሆኑን ይገነዘባል፡፡ ከባለሥልጣኑ የተሰጠው አስተያየት ግን የእስልምና ሐይማኖት ተከታይ ዜጎች በሰላማዊ መንገድ የተቃውሞ ጥያቄ ማቅረባቸውን ገዥው ፓርቲ በበጎ ጎን አለማየቱንና የመብት ጥያቄ የሚያነሱ ዜጎችን ሁሉ ወደ ሽብርተኝነት ፍረጃ ለመክተት የሚያደርገውን ጥረት የሚያመላክት ሆኖ አግኝተነዋል፡፡ በተጨማሪም ገዥው ፓርቲ የእስልምና እምነት ተከታዮችን ኢትዮጵያውያን ዜጎች እንደሆኑ አድርጎ እንደማያያቸውም ሰማያዊ ፓርቲ ተገንዝቧል፡፡
የመንግስት ተወካይ የሆኑት ባለስልጣን በበኩላቸው በሰጡት አስተያየት በሰላማዊ መንገድ ተጠይቆና ታውቆ መንግስት ራሱ ያመነውና እጅግ ሰላማዊ የሆነ የተቃውሞ ሰልፍ እንዲካሄድ ያደረገን ፓርቲ ውጭ የሚገኙ ኃይሎች ተላላኪ አድርጎ ማቅረብ የአብዬን ወደእምዬ እንደሚባለው መሆኑን እየገለፅን ይልቁንም በሕጋዊ መንገድ ተመዝግቦ የሚንቀሳቀሰውን ፓርቲያችንን መንግስት ከልቡ ሊቀበለው እንዳልቻለ አስገንዝቦናል፡፡ በተጨማሪም ይህ አባባል ሰማያዊ ፓርቲን የማይመጥን፤ ፓርቲውም በተግባር እያሳየ ያለውን ሰላማዊ የፖለቲካ እንቅስቃሴ የሚጥስ በመሆኑ አጥብቀን እናወግዘዋለን፡፡ እኝሁ የመንግስት ባለስልጣን በሰላማዊ ሰልፉ የተላለፉት መልዕክቶች ህገ መንግስቱን የሚንዱ ናቸው በማለት በደፈናው ህዝብን ለማታለል ከመሞከራቸው በተለየ የትኛው ሃሳብ የትኛውን የሕገ መንግስት ድንጋጌ እንደሚፃረር ካለማመልከታቸውም በላይ ፓርቲው በፍርድ ቤት ጉዳይ ጣልቃ እንደገባ አድርጎ ለማሳየት መሞከር የመንግስትን ግብር ለሰማያዊ ፓርቲ መስጠት ከመሆኑም ሌላ ላም ባልዋለበት ኩበት ለቀማ ያደርገዋል፡፡
በመጨረሻም የእስልምና እምነት ተከታይ ዜጎቻችን ማንኛውንም የመብት ጥያቄ ከሌሎች ወገኖቻቸው ጋር በሰላማዊ መንገድ የማቅረብ ሕገ መንግስታዊ መብታቸው መሆኑን መንግስትም ሆነ ገዥው ፓርቲ እንዲያውቀው እያሳሰብን፤ ሰማያዊ ፓርቲ ከመንግስትም ሆነ ከገዥው ፓርቲ በሚሰጥ ማንኛውም ማስፈራሪያ ከጀመረው የሰላማዊ ትግል ጉዞ ፍፁም ወደ ኋላ እንደማይል፤ ይልቁንም የተነሱትን የሕዝብ ጥያቄዎች መንግስት በሦስት ወራት ውስጥ ምላሽ እንዲሰጥ አሁንም በድጋሚ ማሳሰብ እንፈልጋለን፡፡
ግንቦት 29 ቀን 2005 ዓ.ም
አዲስ አበባ

No comments:

Post a Comment