Saturday, July 20, 2013

ቅዳሜ ‹‹ፋክት›› በተሰኘ መፅሄት ይዋጃል “ተመስገን ደሳለኝ”

ሲመቸኝ ዝም ብል፣ ዝም ያልኩ መስሎታል፣
ሲታሰብ ነው እንጂ ዝም ማለት የታል፡፡››
እነሆም ይህ የዮፍታሔ ንጉሴ ስንኝ ‹‹የት ጠፋህ?›› ብለው ለተጨነቁልኝ ወዳጅ ዘመድ መላሽ ይሆን ዘንድ ወደድኩ፤
የነገው ቅዳሜ ‹‹ፋክት›› በተሰኘ መፅሄት ይዋጃልና አንባቢያኖቻችን ሆይ ደስታችን ደስታችው ይሁን! ይህ መፅሄት ባለፈው ዓመት ለሶስት ጊዜ ያህል ከታተመ በኋላ በኪሳራ የተዘጋ ነበር፤ አሁን ትንሳኤው ሆኖለት የሚከተሉትን አምደኞች አሰባስቦ ተመልሷል፡፡Temesgen Desalegn Feteh newspaper editor
1.ፕ/ር መስፍን ወ/ማርያም፡-
ሀ/ የመንግስትን ስም ማጥፋት፤ ክቡርነታቸው ናቸው መንግስት?
ለ/ ምንም ይሁን ምን፣ የትም ይሁን የት አበሻ መናገር ይወዳል
(ሁለት የተለያየ ፅሁፍ)
2.ተመስገን ደሳለኝ፡-
ሀ/ ብርቱው ሰው! /The Iron Man/
ለ/ ኢህአፓና የገሀነም ቅፅሩ!
(ሁለት የተለያየ ፅሁፍ)
3.ሙሉነህ አያሌው፡- ለውጥ አለ ወይንስ…?
4.ሐይለመስቀል በሸዋምየለ፡- በብሄርተኛ ልሂቃን የምትታመስ አገር
5.ዳዊት ታደሰ፡- ኡጃማ፡ የብርቱካን መንገድ
6.አቤ ቶኪቻው፡- ሀገራችንን ኢህአዴግ አክራሪነት እንደሚያሰጋት ተሰጋ!
7.ደ/ር በድሉ ወቅጅራ፡- ሀገሬ ገመናሽ (ክፍል አራት)
8.ብርሃኑ ደቦጭ፡- የመለስ ውርሶችና ለሀልዮት የማይመቸው የኢህአዴግ ተፈጥሮ
9.እንዳለጌታ ከበደ፡- ቆራሌው፡- ነባር ልሂቃንን ፍለጋ
10.ቴውድሮስ ተ/አረጋይ፡- ለጌኛዎቹ ሳር ስጧቸው
እና የተለያዩ ፀሀፊያን ተሳትፈውበታል፡፡ ከዚህ በኋላም ዘውትር ቅዳሜ በየሳምንቱ አንባቢያን እጅ ትደርሳለች ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡
ማስታወሻ ለሪፖርተር ጋዜጣ
ሐምሌ አስር ረቡዕ በወጣው ህትመት ላይ ‹‹‹የነፃነት ዋጋ ስንት ነው?› ዥንጉርጉርነት›› በሚል ርዕስ በተለይ ደግሞ ‹‹ያላነበቡ ገምጋሚዎች›› በምትለው ግልገል ርዕስ ስር የተካተተው ሃሳብ ቅንነት የጎደላው ብቻ ሳይሆን ፍፁም በሬ ወለደ መሆኑን ስገልፅ ከጥልቅ ሀዘን ጋር ነው፡፡ በዕለቱ አቶ ግርማ ሰይፉ ‹‹የነፃነት ዋጋ ስንት ነው?›› በሚል ርዕስ ያሳተመው መፅሀፍ የምረቃ ፕሮግራም በውሃ ልማት አዳራሽ መካሄዱ እውነት ቢሆንም እኔ የተገኘሁት የመፅሀፉ ገምጋሚ ተደርጌ እንደሆነ የተገለፀው ግን ውሸት ነው፤ ምክንያቱም የእኔ ድርሻ ከመፅሀፉ ውጪ ያለውን የግርማን ስራዎችና ወቅታዊ ሁኔታ ላይ መናገር ብቻ መሆኑን አስቀድሜ ከአዘጋጆቹ ጋር ስምምነት ላይ ደርሼአለሁ፡፡ የመድረክ መሪውም መፅሀፉ ትላንት ማታ እንደደረሰኝና እንዳላነበብኩት ተናግሮ ነው ወደ መነጋገሪያው የጋበዘኝ፤ እኔም መፃሀፉ ትላንት ምሽት እንደደረሰኝና ለማንበብ እንዳልቻልኩ ከተናገርኩ በኋላ፤ ምንም እንኳ ከመፅሀፉ ውጪ ባሉ ጉዳዮች ላይ ተናጋሪ ሆኜ ብጋበዝም፣ በቂ ምክንያት ቢኖረኝም ሳለናበው በመምጣቴ እናንተን ይቅርታ መጠየቅ ተገቢ ሆኖ ስላገኘሁት ‹‹ይቅርታ እጠይቃለሁ›› በሚል መግቢያነው ንግግሬን የጀመርኩት፡፡
ታዲያ ሀቁ ይህ ሆኖ ሳለ ሪፖርተር ጋዜጣ ከየት አምጥቶት ይሆን ‹‹ይህንን መፅሀፍ የገመገሙት ዶ/ር ኃይሉ አርዓያና ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ናቸው›› ያለው? ስለቀጣዩ ምርጫ ዋጋ ቢስነትም የተናገርኩት መፅሀፉን ጠቅሼ ሳይሆን ከስርዓቱ ጉልበተኝነት ተነስቼ መሆኑንም ሪፖርተር እንዴት ሊሳተው እንደቻለ ግራ አጋቢ ነው፡፡ ‹‹ተቃዋሚዎች ለመሞት እንጂ ለመግደል አልተዘጋጁም›› የሚል ቃል እንዳልወጣኝም በአዳራሹ የተሰበሰበው ሰው ሁሉ የሚያውቀው ነው፤ (በነገራችን ላይ ይህንን የምለው ከፍርሃት አይደለም፤ ውሸት ስለሆነ ብቻ ነው) እኔ በዕለቱ የተናገርኩት ‹‹ለስርዓት ለውጥ ምርጫን የግድ ጠብቁ የሚል ህግ የለም፤ አገዛዙ ካልተመቸን አደባባይ ወጥተን ቤተ-መንግስቱን ነቅንቀን ለውጥ ማምጣት አለብን፤ ይህ ማንም የማይሰጥን፣ ማንም የማይነሳን መብታችን ነው፤ መልካምነቱ ደግሞ በሰላማዊ ትግል ውስጥ መሞት እንጂ መግደል የለም፤ መታሰር እንጂ ማሰር የለም፤ አካል መጉደል እንጂ አካል ማጉደል የለም፤ መዘረፍ እንጂ መዝረፍ የለም…›› ነው ያልኩት፡፡ ከሁሉም የሚገርመው የጋዜጣው ነጭ ውሸት ‹‹‹በ2006 ዓ.ም ተቃዋሚዎችን ከውጪ ሆነን ከማየት ወጥተን ትግሉን እናፋፍመው› የሚለው ንግግሩ በከፍተኛ ጭብጨባ የታጀበ ነበር፡፡ በማጠናቀቂያ አስተያየቱም ‹መፅሀፉን ባላነበውም ዶ/ር ኃይሉ አርዓያ እንደነገሩን…› ሲል ሲያጨበጭቡለት የነበሩትን ታዳሚዎች ያሳዘነ ነበር፡፡ በወቅቱ ሪፖርተር ያነጋገራቸው አስተያየት ሰጪዎችም ይህንን ቅሬታ ነው የገለፁት›› የሚለው ነው፤ መቼም እነዚህ ሰዎች ኢቲቪ ‹‹አንዳንድ ነዋሪዎች…›› እያለ የሚጠቅሳቸው ስም፣ ፆታ፣ አድራሻ፣ ዜግነት ያሌላቸው፣ እነዛ የማይጨበጡት፣ የማይዳሰሱት፣ የማይናገሩት… ሰዎች ካልሆኑ በቀረ ዕድምተኞቹ የተናገርኩትን በሚገባ ሰምተዋል፡፡
በመጨረሻም ስለማይመቸኝ መከራከሪያ፡-
ሪፖርተር በወቅቱ ያነጋገራቸው ሰዎች ‹‹ተቃዋሚ ነው ወይስ ጋዜጠኛ?›› የሚል ግርምት የሚያጭር ጥያቄ እንዳቀረቡለት ገለጿል፡፡ ይህ ግን ምን ማለት ነው? ጋዜጠኛ ሀገር የለውም፣ የፖለቲካ አቋም የለውም ያለውስ ማን ነው? እሺ! ሌላው ይቅር ይህ ሁሉ የመንግስት እና ‹‹ቅምጥ›› ጋዜጠኛ ‹‹ኢህአዴግ ጌታ ነው›› ሲል መዋሉን ስለምን ሪፖርተርን አላሳሰበውም? ወይስ ጋዜጠኛ የስርዓቱ ደጋፊ ብቻ ነው መሆን የሚችለው የሚል አመክንዮ አለ?
የሆነ ሆኖ አዎ! እኔ ጋዜጠኛ ነኝ፤ አዎ! የስርዓት ለውጥ የሚፈልግ የገዥው ፓርቲ ተቃዋሚ ነኝ-ሀገሬን እየገዳለት ነውና፤ አዎ! አደባባይ መውጣት ከምርጫም ይሁን ከሌላ በላይ ቅድሚያ እንደሚሰጠው ደጋግሜ እናገራለሁ፤ በ2007 ዓ.ም ለሚደረገው ምርጫም (ምን አልባት ኢህአዴግ በእኛ ድክመት እስካዛ ድርስ ከቆየ ማለቴ ነው) ፕ/ር መርጋ በቃና የሚመራውን ምርጫ ቦርድ ተማምኜ በፍፁም የምርጫ ካርድ አልወስድም፡፡ ምክንያቱም አደባባይ በመውጣት መሬት አርድ ህዝባዊ ንቅናቄ ፈጥሮ ለውጥ ለማምጣት እንጂ ለመምረጥና ለመጭበርበር አልተዘጋጀውምና፤ በአናቱም እውነት እውነት እላቸኋላሁ ከዚህ በኋላ ታሪክ ለመቀየር ብዙ እንጠብቅም፡፡
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!

No comments:

Post a Comment